Ecclesiastes 11

እንጀራ በውሃ ላይ

1እንጀራህን በውሃ ላይ ጣል፤
ከብዙ ቀን በኋላ መልሰህ ታገኘዋለህና።
2ሀብትህን ሰባት ቦታ፣ እንዲያውም ስምንት ቦታ ከፍለህ አስቀምጥ፤
በምድሪቱ ላይ የሚመጣውን ጥፋት አታውቅምና።
3ደመናት ውሃ ካዘሉ፣
በምድር ላይ ዝናብን ያዘንባሉ፤
ዛፍ ወደ ደቡብም ሆነ ወደ ሰሜን ቢወድቅ፣
በወደቀበት ቦታ በዚያ ይጋደማል።
4ነፋስን የሚጠባበቅ አይዘራም፤
ደመናትንም የሚያይ አያጭድም።

5የነፋስን መንገድ እንደማታውቅ፣
ሕይወት ወይም መንፈስ በእናት ማሕፀን ውስጥ ወደሚገኘው አካል እንዴት እንደሚገባም
ወይም አካል በእናት ማሕፀን ውስጥ እንዴት እንደሚሠራ እንደማታውቅ ሁሉ
እንደማታውቅ ሁሉ፣
ሁሉን ሠሪ የሆነውን፣ የእግዚአብሔርን ሥራ
ማስተዋል አትችልም።

6ጧት ላይ ዘርህን ዝራ፤
ማታም ላይ እጅህ ሥራ አይፍታ፤
ይህ ወይም ያ፣
ወይም ሁለቱ መልካም ይሁኑ፣
የቱ እንደሚያፈራ አታውቅምና።

ወጣት ሳለህ ፈጣሪህን ዐስብ

7ብርሃን መልካም ነው፤
ፀሓይንም ማየት ለዐይን ደስ ያሰኛል።
8ሰው ምንም ያህል ብዙ ዓመት ቢኖር፣
በእነዚህ ሁሉ ይደሰት፤
ነገር ግን ጨለማዎቹንም ቀናት ያስብ፤
እነርሱ ይበዛሉና፤
የሚመጣውም ነገር ሁሉ ከንቱ ነው።

9አንተ ወጣት በወጣትነትህ ጊዜ ደስ ይበልህ፤
በወጣትነትህም ዘመን ልብህ ደስ ያሰኝህ፤
የልብህን መንገድ፣
ዐይንህ የሚያየውንም ሁሉ ተከተል፤
ነገር ግን ስለ እነዚህ ነገሮች ሁሉ፣
እግዚአብሔር ወደ ፍርድ እንደሚያመጣህ ዕወቅ።
10ስለዚህ ጭንቀትን ከልብህ አርቅ፤
ክፉ ነገርንም ከሰውነትህ አስወግድ፤
ወጣትነትና ጕብዝና ከንቱ ናቸውና።
Copyright information for AmhNASV